onsdag 13. mai 2015

ሰማያዊ ፓርቲ vs የኦሮሞ ህዝብ

በርግጥ በዚህ ወሳኝ ጊዜ ላይ መነካካት የሌሉብን ጉዳዮች እንዳሉ አምናለሁ። በዚያው ልክም አሁን ያለውን የህዝባችንን ስሜት በመጠቀም አንዳንድ ልታለፉ የማይገባቸው ወቅታዊና አንገብጋቢ ነገሮችን መጠቆምም ደግሞ ይጠቅማል የሚል እምነት አለኝ። በዚህ የምርጫ ግርግር ውስጥ አያሌ ጉዳዮች ወደ ህብረተሰባችንም ሆነ ወደ አገራችን የሶሽዮ-ፖለቲካ ከባቢ አየር ሾልከው በመግባት ሳይስተዋሉ የሚያልፉበት አጋጣሚ ቢኖርስ? የህዝባችን ትኩረት ወያኔን በማስወገድ ላይ ብቻ ሙሉ በሙሉ መጠቃለል የለበትም። ግራና ቀኝ እንዲሁም ኋላችንን በጥንቃቄ እየቃኘን መሄድ ግዴታ ይሆናል። በተለይ የኦሮሞ ህዝብ የኢትዮጵያ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ጂኦግራፊያዊ መሠረትና እምብርት እንደመሆኑ መጠን የአገሪቱን ሁለንተናዊ እንቅስቃሴዎች በከፍተኛ ማስተዋል መከታተል እንደሚጠበቅበት ግልጽ ነው። ሀገሪቱ ላለፉት መቶ ምናምን አመታት በወሰደቻቸው እርምጃዎች፤ በተከተለቻቸው ፖሊሲዎች፤ ባስተላለፈቻቸው ውሳኔዎች ወዘተ በግንባር ቀደምትነት የተጎዳው የኦሮሞ ህዝብ ነው።
የኦሮሞ ህዝብ "በቁመቱ ልክ" (ዶ/ር መረራ እንደሚሉት) የሆነ የፖለቲካ "ስፔስ" ያስፈልገዋል። ከበቂ በላይ ለሆነ ጊዜ በማያፈናፍኑ ሥርዓቶች ውስጥ እንደማለፋችን ከእንግዲህ ለዚህ አይነት የፖለቲካ ጨዋታዎች የሚሆን ጫንቃ በፍጹም ሊኖረን አይችልም። ነገሮች ሁሉ በግልጽና በጉልህ ብቻ መከናወን ያለባቸው ጊዜ ላይ ነው ያለነው። ይህ ማለት ማንኛውም ቡድንም ሆነ ሥልጣን ላይ የተቆናጠጠ አካል በህዝብ ጥቅም፣ ታሪክ፣ ባህልና ማህበራዊ እሴቶች ላይ እንዳሻው የሚናገርበት ጊዜ ላይመለስ አልፏል ማለት ይሆናል። በዚህች ጽሁፍ አጠር ባለ መልኩ ሰማያዊ ፖርቲን ማስጠንቀቅ የሚፈልገው ጉዳይ ወርወር ማድረግ አስቤ ነው። ሰማያዊዎች በኢትዮጵያችን ከተነሱ ብዙ ፓርቲዎች ለየት የሚያደርጋቸው ከጥቂት በላይ ባህሪያት ቢኖራቸውም እኔ ግን በቀጥታ የኦሮሞን ህዝብ ይመለከታሉ በሚላቸው ላይ አተኩራለሁ።
"ሰማያዊ ፓርቲ ሰማይ ላይ ነው ያለው፤ ገና ወደ ምድር ወርደው በመሬት ላይ ያለውን የሀገራችንን ሁለንተናዊ ጉዳዮች አልተረዱም፤ ስለዚህ ትንሽ ጊዜ ያስፈልጋቸዋል" ያለው ማን ነበረ? ስለሰማያዊ ፓርቲ ብዙ በማለት ጊዜዬን አላጠፋም። የፓርቲውን የፖለቲካ አቅጣጫ ለመገንዘብ አቶ ይልቃል ጌትነት (ይቅርታ ኢንጂነር ስላላልኩ) በተለያዩ ጊዜያት ያደረጓቸውን ንግግሮች አንድ በአንድ ማጤን በቂ ይሆናል። የፓርቲው ግንባር ቀደም ዓላማ የኦሮሞን ህዝብ "ኢንተረስቶች" አንድ በአንድ ማናናቅ፣ መጋፈጥና በተቻለ አቅም ሁሉ መቀልበስ ይመስላል። ይህንን ደግሞ በተደጋጋሚ አይተናል። ለምሳሌ የአኖሌና የጨለንቆ ጭፍጨፋዎችን ለማስታወስ የተሰሩትን የመታሰቢያ ሀውልቶች ሰማያዊ ፓርቲ ይቃወማል። የኦሮሞን ህዝብ በቀጥታ ይጠቅማል ተብሎ የሚታመነውን በቋንቋ ላይ የተመሰረተ የፌደራል ሥርዓት ሰማያዊ ፓርቲ አይቀበልም። ይህንንም ለኦሮሚያ እውቅና እንደመስጠት አድርገው ያዩታል። እንደ ኢህአፓ እና ቅንጅት ሁሉ ፍንፍኔን መሠረት አድርጎ የተነሳው ሰማያዊ ፓርቲ ከወያኔ ሥርዓት ባልተናነሰ መልኩ ለኦሮሚያ እጅግ ፈታኝ የሆነ የፖለቲካ ባህል ለመፍጠር በትጋት እየሰራ ለመሆኑ ህዝባችን ምሥክር ነው። ያለፉት ሥርዓቶች አፍቃሪና አቀንቃኝ በሆኑ ግለሰቦች የተሞላውና የሚደገፈው ይሄው ፓርቲ በኦሮሞዎች ዘንድ እንዴት ሊገመገም እንደሚገባውም ለውይይት መቅረብ ያለበት ጉዳይ መሆኑ ሊሠመርበት ይገባል። የሰማያዊ ፓርቲ ደጋፊዎች ምናልባት ከወያኔ ደጋፊዎች ጋር ብዙ የሚጋሩዋቸው ነጥቦች (በተለይ ኦሮሞን በመጫን ረገድ) እንዳላቸው ይታወቃል። የኢህአዴግና የሰማያዊ ፍጥጫም ከሥልጣን ፉክክር የዘለለ አይደለም።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በዘንድሮው ምርጫ ኦሮሞዎች ሰማያዊ ፓርቲን ከመምረጥ እንዲታቀቡ ይመከራሉ። ሰማያዊዎች ይህችን የምርጫ ወቅት ለማለፍ አንዳንድ የማታለያ ሀሳቦችን ሊጠቀሙ ቢሞክሩም አጀንዳቸው በአጠቃላይ በጸረ-ኦሮሞ መርሆዎች ላይ መዋቀሩን ልንዘነጋው አይገባም። በመሆኑም ኦፌኮ/መድረክ በሚወዳድርባቸው ክልሎች ሁሉም ኦሮሞ ድምጹን ለመድረክ እንዲሰጥና በማንኛውም ሁኔታ ቢሆን ሰማያዊን እንዳይመርጥ ጥሪዬን አስተላልፋለሁ።

Abdii Gemechu

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar