onsdag 10. august 2016

ለራበው ሰው ብትዘምርለት የሚሰማህ በጆሮው ሳይሆን በሆዱ ነው

ንድ ‹‹ሕዝባዊ ነኝ›› የሚል አካል፡- ሕዝብ የሚለውን ካልሰማ... ነገር ግን በሕዝቡ ዘንድ መደመጥን ከጠበቀ ፣ ሕዝቡን የንቀት በሚመስል እይታ እያየ... ነገር ግን ከሕዝቡ ዘንድ ክብርንና ፍቅርን ከፈለገ ፣ ሕዝቡ ‹‹ስህተት ነህ›› እያለው... በደፈናው ‹‹ትክክል ነኝ›› ካለና ትክክልነቱን ማስረዳትም ማሳመንም ከተሳነው ፣ ሕዝቡ ‹‹ያልተመለሱ ጥያቄዎች አሉኝ›› እያለው... ‹‹ጥያቄህንም መልስህንም ማውቀው እኔ ነኝ - መልሸልሃለሁም›› ካለ፣ ሕዝቡ ‹‹ብሶቴን ልገልጽ አደባባይ ወጥቻለሁ›› እያለው... ‹‹የት አለህ የሚታዩኝ ጥቂት አንተን የማይወክሉ ሰዎች ናቸው›› ብሎ ከመለሰለት...... በቃ ይህ አካል ወይ ሆን ብሎ ሕዝቡን ለማናደድ እየተናገረ ነው ወይም ደግሞ ‹‹የሚታዩም ሆነ የሚነገሩ መልእክቶች ተቃራኒ የሚሆኑበት ልዩ ፍጡር›› ነው፡፡ የመጀመሪያውን ከሆነ (ሆን ብሎ ሕዝብን ለማናደድ ከተናገረ) ወደ አእምሮው ይመለስና ሕዝቡን ይቅርታ ይጠይቅ፡፡ ሁለተኛውን (መልእክቶች ሁሉ በተቃራኒው የሚደርሱት ፍጡር) ከሆነ ግን በግልጽ ይታወቅና ሕዝቡ በጸሎትም ሆነ በህክምና ወደ ትክክለኛ ሰውነት ይመለስ ዘንድ ያግዘው፡፡ ከዚህ በተረፈ ግን (እኔ በግሌ) ከምሰማው ይልቅ የማየውን የማምን ጤነኛ ሰው ስለሆንሁ (እግዚአብሔር ይመስገንና) በዚህ ሰዓት በሀገራችን ሕዝባዊ እምቢተኝነትና ግልጽ ተቃውሞ የለም የሚለውን አልቀበለውም፡፡ መሠረቱ ምንም ይሁን ምን፣ ከጀርባ ሌላ አካል ኖረም አልኖረም፣ በሌሎች መገለጫዎች ጠራነውም አልጠራነውም... በግልጽ የሚታይና ኃላፊነት የሚወስድ አካል እንኳን ባልኖረበት... አሁን ካለበት ደረጃ የደረሰና የሚቀጥልም የሚመስል ሕዝባዊ ተቃውሞ አለ፡፡ ያውም ሞት እንኳን ሊመልሰው ያልቻለና አንድ ሰው በሞተ ቁጥር እየተባዛና እየተፋፋመ እየሄደ ያለ ተቃውሞ፡፡ እንዲያውም በእኔ ዕድሜ ካየኋቸውም ሆነ በታሪክ ካነበብኋቸው ኢትዮጵያዊ የሕዝብ ተቃውሞዎች ሁሉ በዚህ መልኩ በስፋትና በተከታታይነት የተካሄደ የለም ባይ ነኝ፡፡ ከሐቁ መራቅና ሌላ ፍረጃ መስጠት መፍትሔ አይመስለኝም፡፡ እንዲያውም የበለጠ ወደተውሰበሰበ ችግር ውስጥ ነው የሚከተን፡፡ እንዲያውም... እንዲያውም..... የመፍትሔ አካል ሊሆኑ የሚችሉ ግለሰቦችንም ሆነ ድርጅቶችን የበለጠ የሚያስከፋና ተስፋ የሚያስቆርጥ ነው የሚሆነው፡፡ ለሚያስተውልና ልባም ለሆነ ሰው ደግሞ ይህ በራሱ የሌላ መጻኢ-ችግር መነሻ ነው፡፡ ባለመፍትሔዎች ተስፋ የቆረጡና ዝም ያሉ ዕለት... ያኔ መላ ቅጡ ይጠፋና ማጣፊያው ያጥረናል፡፡ የምናገረው ዝም ብሎ የቅዠት ትንበያ አይደለም፡፡ በመረዳት እቅሜ ልክ የተረዳሁትን መፍትሔ አዘል ሐቅ እንጅ፡፡ የሚሰማ ኖረም አልኖረም... እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ወጣት የሀገሬ ጉዳይ ያገባኛልና የማስተውለውን እውነት በተላዘበ መልኩ ከመግለጽና መፍትሔዎችን ከመጠቆም አልቦዝንም፡፡ ማንም ሊጠቀምበት ባይችል እንኳን ለእኔ የአዕምሮ ዕረፍት ስል እናገራለሁ፡፡ የእኔ ሐሳብ ብቻ ነው ትክክል አልልም፡፡ ነገር ግን... ሐሳቦችን የመናቅና ያለመቀበል፣ በራሳችን መንገድ ብቻ የመሄድ አባዜ ካተጠናወተን በቀር... ከእንደኔ ዓይነቱ ጀምሮ በብዙዎች የሚወጣጡ ሐሳቦች ናቸው ተደምረው መፍትሔ የሚሆኑት፡፡ የምንባለውን እየናቅን ጆሮ ባልሰጠን መጠን ወደ ባሰ ችግር እየገባን መሆኑን ማስተዋልም ትልቅነት ነው፡፡ በእኔ እምነት... ከምንም ነገር በፊት ለዚህ ሕዝባዊ ተቃውሞ እውቅና መስጠት ያስፈልጋል፡፡ ከዚያም ሕዝቡ ራሱ የመፍትሔ አካል እንዲሆን ነፃ እናድርገው፡፡ ‹‹ጉዳዬና ችግሬ›› ላለው ነገር እውቅና ካልሰጠንለት ሕዝብ ጋር መደራደር ብሎ ነገር አይገባኝም፡፡ እውቅና በነፈግነውና ሌላ ስም በሰጠነው መጠን እየተባባሰ የሄደ እንጅ የረገበ ነገር እንደሌለ እያየን ይመስለኛል፡፡ ሕዝቡ በተግባር ያለበትንና የሚሳተፍበትን ጉዳይ ‹‹ያንተ አይደለም፣ የለህበትም...›› በማለት ብቻ መፍትሔ አመጣለሁ ማለት... ከንቱ ድካምና ሕዝቡንም መናቅ ነው፡፡ ይህን ሕዝብ ‹‹ነገሮችን የመረዳትም ሆነ ራስህ የምታደርገውን እንኳን የማወቅና የመተርጎም ችግር አለብህ›› እንደማለትም ነው፡፡ ትክክለኛ ጥያቄውን በመመለስ እንጅ ‹‹ለመሞት ቆርጦ ወደወጣ ሕዝብ›› የታጠቀ ፖሊስ በመላክ የሚመጣ መፍትሔ... ለእኔ አልታይህ ብሎኛል፡፡ ይህ ዓይነቱ እርምጃ ከመፍትሔነቱ ይልቅ ችግርነቱ ያመዝንብኛል፡፡ ራበኝ ላለ ሰው ምግብ እንጅ ሙዚቃ አይጋበዝም፡፡ ‹‹ለራበው ሰው ብትዘምርለት የሚሰማህ በጆሮው ሳይሆን በሆዱ ነው›› የምትለዋን የአባቶቻችንን አባባል ልብ ይሏል፡፡ ‹‹ጠቢብ ከሌሎች ስህተት ይማራል›› የሚለውንም እንዲሁ፡፡ በአለማየው ግርማ

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar